Sunday, October 29, 2017

« አውሮራ » - የጦርነት አረር ፣ የፍቅር ቀለሃ


ሪኩ የተገነባው ዙዎቻችን በምናውቀው እውነት ላይ ነው ። ጠላትህ ጠላቴ ነው ተባብለው የተማማሉ ሁለት ብሄርተኛ ቡድኖች ለረጅም አመታት ታግለው እንደ ሀገር የሚያስበውን ቡድን አሸንፈው ስልጣን ያዙ ።

በስልጣን ማግስት ሀገር የፈለገውን ይበል ብለው መስመር ባለፈ ፍቅር ከነፉ ። እንደ ደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ‹ ሁለት አፍ ያለው ወፍ › ሆኑ ። በፍቅር ተጎራረሱ ። ተቃቅፈው በረሩ ፣ አለም ጠበባቸው ... ተጣብቀው ዘመሩ ‹ አይበላንዶ  ...  › እያሉ ።ተያይዘው ፈከሩ ! ‹ ነፍጠኛ ሰመጠ ፣ ተራራ ተንቀጠቀጠ › በማለት ... አብረው ተዛበቱ ‹ ትግል ያጣመረውን ህዝብ አይለየውም › በሚል ስልቂያ ... ኪስህ ኪሴ ነው ፤ ሚስትህ ሚስቴ ናት ፤ ግዛትህ ግዛቴ ... ምን ያልተባባሉት አለ ?

 ከአይን ያውጣችሁ ያላቸው ግን አልነበረም ።

እየቆየ አይንና ናጫ ሆኑ ... በአጎራረስህ እየተጎዳው ነው በሚል አንደኛው አፍ የጫካ ውንድሙን ካደ ። የእህል ምርቱንም ሆነ የሚያጌጥበትን ማእድን ደበቀ ። የብር ኖቶችን ቀየረ ፣ የድንበር ንግድ ግብይት በዶላር እንዲሆን ድንገተኛ ህግ አረቀቀ ። ይህ ተግባር ለሁለተኛው አፍ የማይታመን ክህደት ነበር ። ባጎረስኩ እጄን ተነከስኩ አለ ። ጠፍጥፎ በሰራው ልጅ ተናቀ ... ሹካ አያያዝ አስተምሬው ? በኔ ደም ለወንበር በቅቶ እንዴት ክብሬን ያራክሳል በማለት ለጦርነት ተዘጋጀ ።

‹ አውሮራ › ይህን የምናውቀውን ታሪክ ይዞ ነው መዋቅሩን የገነባው ። የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት እንዴት ተጀምሮ እንደምን እንዳለቀ እናውቃለን ፣ ምን እንዳስከተለም የብዙ ወገኖች መረጃ አለን ። የመንግስት ሚዲያዎችን ጨምሮ የድርጅቶቹ ልሳኖች የአውደ ውጊያውን ታሪክና የታሪክ ሰሪ ሰዎችን ህይወት በመዳሰስ አታካች በሆነ መልኩ በተከታታይ አቅርበውልናል ። ታዲያ አውሮራ ምን የተለየ ነገር ሊነግረን ታሪክ ቀመስ ልቦለድ ሆነ ? ቢባል ትክክል ነው ።

ደራሲው ሀብታሙ አለባቸው ግን ብልህ ነው ፣ ገና በጠዋቱ ፣ ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ያስተዋወቀንን የታሪክ በከራ እንዴት ሳይሰለች እያጠነጠነ እስከ ምዕራፍ 43 መዝለቅ እንዳለበት በሚገባ ተረድቷል ። ስለተረዳም ሳቢና ተነባቢ አደረገው ።

ይህን ለማከናወን ከረዳው ስልት አንደኛው የትረካውን ኳስ ለመለጋት በመረጠው የመቼት አንግል የተወሰነ ይመስለኛል ። ደራሲው 80 ከመቶ የሚሆነውን ታሪክ የሚያቀብለን ከኤርትራ አንጻር ሆኖ ነው ። በትረካው የአስመራን ውበት ፣ የወታደራዊ ካምፖችን ሚስጢር ፣ የደህንነት ተቋማት ፕሮፓጋንዳ ፣ ሳዋ ስለተባለው የሰው ቄራ ፣ የፕሬዝዳንቱን ጽ/ቤት ከነተግባርና ግዴታቸው እንመለከታለን ። የህዝቡን አበሻዊ ጥላቻ ፣ ፖለቲካዊ ሹክሹክታ እና ስነልቦና እንመረምራለን ። የባለስልጣናቱን በተለይም የፕሬዝዳንቱን እምነት ፣ አስተሳሰብ እና ፍላጎት እንታዘባለን ። በአጠቃላይ ከአስመራ የምናገኘው አዲስ መረጃ ታሪኩ ሰቃይና አጓጊ እንዲሆን ትልቅ ሚና ተጫውቷል ። የታሪኩ ልጊያ ከአስመራ እየተነሳ ወደ ኢትዮጽያ ፣ ጅቡቲና ሌሎች አካባቢዎች ሲያመራ ደግሞ ተዝናኖት ብቻ ሳይሆን አማራጭ እሳቤ ይፈጥርልናል ። በመሆኑም የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት አዲስ ሆኖ እንዲሰማን አድርጓል ።
ሌላም አለ ። ታሪኩን የሚደግፉት የሴራ ቅንብሮች ባለሁለት አፍ ወፎቹ ይፋ በሆነ መልኩ በመድፍ እንዲቆራቆሱ ብቻ አይደለም የሚያደርገው - ወፎቹ በየሰፈራቸው በተዳፈነው ረመጥ እንዲለበለቡም ጭምር እንጂ ።

የአስመራው ወፍ / ኢሳያስ / ክብሩንና ጥቅሙን ለማስጠበቅ መጠነ ሰፊ ፣ የተደራጀና ህቡዕ ተኮር እንቅስቃሴ ያደርጋል ። ኢትዮጽያዊው ወፍ / መለስ / አንድም አናት አናቱን ከሚጠቀጥቁት ወንድም ግንደ ቆርቁሮች በሌላ በኩል ከሩቅ አጎቱ የሚወረወርበትን ሞርታር ለመከላከል መከራውን ሲበላ እንመለከታለን ።

በነገራችን ላይ ከአስመራ ወደ ኢትዮጽያ የሚጋልበው የታሪክ ጅረት ሁለት መቆጣጠሪያ ቤተመንግስቶች አሉት ። የአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ እና የአቶ ሃይላይ ሃለፎም ። በፍትህ ሚ/ሩ አቶ ሃይላይ ቤት አራት የታሪኩ ቁልፍ ሰዎች ይገኛሉ ። ቤተሰቦች ናቸው ። ሳህል በረሃ የተወለደችው ፍልይቲ ፣ ወንድሟ ሰለሞን እና ባለስልጣን እናታቸው አኅበረት ። ሃይላይ በርግጥም ለሰላምና ፍትህ የቆመ ብቸኛ ሚኒስትር ነው ። ከኢትዮጽያ ጋር የሚደረገው ጦርነት መሰረት የሌለው የዜሮ ድምር ፖለቲካ በመሆኑ መቆም አለበት በሚለው አቋሙ ከዋናው ቤተመንግስት ሰውዪ ጋር ይጋጫል ።

በሌላ በኩል ኢሳያስ የሃይላን ልጅ ፍልይቲን እንደ ጆከር ሲጠቀምባት እናያለን ። ኢ/ያ ውስጥ የሚከናወነውን የዶላር ዘረፋ ፣ የስለላ ስራና ህቡዕ ግድያ ትመራለች ። በጅቡቲ ወደብ ወደ ኢ/ያ የሚገባውን ስትራቴጂካዊ ንብረት ለማውደም ተመራጭዋ ሰው እሷ ናት ። ባድመ በመዝመት ለሌሎች ያስቸገሩ የመረጃና የተመሰጠሩ መልእክቶችን የመፍታት ስራ ትሰራለች ። ፍልይቲ የፕሬዝዳንቱ ቀኝ እጅ ፣ ብሩህ አእምሮ ያላት ፣ ደፋር ፣ አፍቃሪ እና ጨካኝ ገጸባህሪ ናት ።

ከኤርትራ ህዝብ አንጻር / አማራ ጠላት ነው የሚል ቆሻሻ ሀሳብ / ግን አንድ ይቅር የማይባል ክህደት ትፈጽማለች ። ክህደቱ ለኤርትራ የቴሌ እና ኤሌክትሮኒክስ ግንባታ ትልቅ ድርሻ ያከናወነውን ኢትዮጽያዊ ሰው በማፍቀሯ ነው ። አስራደ ሙሉጌታ ይባላል ። ሻእቢያ ጉልበቱንና እውቀቱን እንደ ሽንኮራ ከመጠጠው በኋላ ሊያስወግደው ቀነ ቀጠሮ ይዞለታል ። ለአስመራ ፖለቲካ ትልቅ አይን የሆነችው ፍልይቲ ከመንግስታዊው ተልዕኮ ጎን ለጎን ፍቅረኛዋን ለማዳን ህቡዕ ትግል ስታከናውን እንመለከታለን ። የሃይላይ ወንድ ልጅ ሰለሞን ‹ ናጽነት › በሚለው ነጠላ ዜማው በከተማው የታወቀ ዘፋኝ ሆኗል ። ሙዚቃው ማዝናኛ ብቻ ሳይሆን የዘመቻ መቀስቀሻም ነው ። ናጽነት ብሎ የዘፈነው ግን በኢሳያስና በአባቱ ለተመራው ትግል ማስታወሻ ለመስራት ብቻ አይደለም ። እንደውም በዋናነት የዘፈነው ነጻነት የተባለች ቆንጆ ወጣት በማፍቀሩ ነው ። ነጻነት ለኤርትራ ወጣት የእግር እሳት ወደሆነበት ሳዋ ስትገባ እሱም እንዳላጣት ብሎ ፈለግዋን ይከተላል ። እሷን ፍለጋ ላይ ታች ሲል ነጻነት በሁለት የባደመ ጦር ጄነራሎች አይን ውስጥ ትወድቃለች ። ልክ እንደ ባድመ መሬት ሊቆጣጠሯት ሌት ተቀን ስትራቴጂክ ይነድፋሉ ።

እናም የአንደኛው ቤተመንግስት ሰውዪ ከኢ/ያ ድል ለማግኘት ሲራራጥ ፣ የሁለተኛው ቤተመንግስት አባላት ደግሞ ከራሱ ከኢሳያስ ጭቆና ለመላቀቅ እንዲሁም ፍቅረኛዎቻቸውን ለመታደግ ላይ ታች ሲሉ በታሪኩ ተወጥረን እንያዛለን ።

መጽሐፉ ጥቃቅን ቴክኒካል ችግሮች የሉበትም ማለት አይቻልም ፣ ለአቅመ ግነት የሚበቁ ስላልመሰለኝ ዘልያቸዋለሁ ። ይልቁንስ ደራሲው የራሱ እምነት የሚመስል ጉዳይ መጀመሪያ ምዕራፍ ላይ ቆስቁሶ እንዲረሳ ወይም እንዲጨነግፍ ማድረጉ የሚቆጭ ይመስለኛል ። ያነሳቸው ጥያቄዎች የአንባቢም መሰረታዊ ጥያቄዎች ሊሆኑ የሚችሉ ናቸው ። የባርካ ማተሚያ ቤት ባለቤት የሆኑ ግለሰብ አቶ ሃይላይ ሊጽፉ ባሰቡት መጽሐፍ ውስጥ አራት መሰረታዊ ጥያቄዎችን አዳብረው አንዲሰሩ ሀሳብ ያቀርባሉ ። ከቀረቡት ሃሳብ ውስጥ ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው ፣

1 . የኤርትራ ነጻነት ትግል ለምን በ 1885 ምጽዋ በኢጣሊያ መያዝን በመቃወም አልተጀመረም ?
2 . ከኤርትራ ልዩ ማንነት የተፀነሰ ትግል ከሆነ ለምን 30 አመታት ፈጀ ?

ደራሲው ስራውን ከሰሩት 285 ሺህ ናቅፋ እንደሚያገኙም ውል ታስሮ ነበር ። ሆኖም የማተሚያ ቤቱ ባለቤት ሲያዙ ፣ አቶ ሃይላይም ሲገደሉ ሃሳቡ ይመክናል ። እንደ ስነጽሁፍ ሃያሲ የሁለቱ ሰዋች መጥፋትን በአስመራ ወስጥ የመጻፍ ፣ የመናገር ፣ የማሰብ እና የዴሞክራሲ መሞትን ለመተርጎም ያስረዳን ይሆናል ። ከዚህ በላይ ግን ታሪኩ ባይጨነግፍ የበለጠ ጠቃሚ ያደርገን ነበር ብሎ መከራከር ያስኬዳል ። አቶ ሃይላይ ለእውነት የቆሙ ገጸባህሪ በመሆናቸው እየመረራቸውም ቢሆን ከኤርትራ ጀርባ የተደበቁ ጉዳዮችን ያነሱ ነበር ። ይሄን አንስተው ቢሞቱ ደግሞ ሞታቸውንም ይመጥን ነበር ። የበለጠ ጀግና መስዎዕት እናደርጋቸው ነበር ።

‹ አውሮራ › ጦርነት ላይ መሰረት አድርገው እንደተሰሩት ልቦለዶቻችን ማለትም ኦሮማይ እና ጣምራጦር የተሳካ ስራ ነው ። ድንበር ያቆራርጣል ፤ እዚህና አዚያ እንደ ቴኒስ ኳስ ሲያንቀረቅበን ጨዋታው ሰለቸኝ ብለን ከሜዳው ዞር ማለት አንችልም ። ፈጣን ነው ፤ በድርጊት የተሞላና በመረጃ የደነደነ ። መንቶ ነው ፤ ፍቅርና ጦርነትን በእኩል ጥፍጥና ከሽኖ ማቅረብ የቻለ ። ሰባኪ ነው - ፍቅር ያሸንፋል የሚል አይነት ፤ ተዛምዶ ተጋብቶ ተዋልዶ የተካደ ትውልደን የሚያባብል ። የሆነውን ብቻ ሳይሆን  የሚሆነውን ቁልጭ አድርጎ የሚናገር ። በተለይም የአንድነት አሳቢዎችን ገድለን ቀብረናል ብለው ለሚመጻደቁ ጠባቦች « ውሸት ነው ! » ብሎ ጥበባዊ ምስክርነት የሚሰጥ ።

በታሪኩ ውስጥ ማንነቱን ደብቆ ስሙን አቦይ ግርማ አስብሎ ቀን ከለሊት በባድመ የልመና ተግባር የሚያከናውነው እንኮዶ /የደርግ ኮማንዶ የነበረ / አንድ እጁ ስለተቆረጠና አይኑ ስለተጎዳ ማንም ግምት ውስጥ ያሰገባው አልነበረም ። ሆኖም መጀመሪያ የባድመን መሬት ፈልፍለው የገቡ የሻእቢያ ወታደሮችን ፣ በመጨረሻም እጁን በመጋዝ ቆርጦ የጣለውን ጄኔራል ግዜ እየጠበቀ መበቀል ችሏል « ለገንጣይና ጡት ነካሽ ዋጋው ይሄ ነው » እያለ ። ይህ ትርክት በስነጽሁፍ ቋንቋ ፎርሻዶው ወይም ንግር የሚባለው ቴክኒክ ነው - ነገ እንዲህ መሆኑ አይቀርም ለማለት ።



No comments:

Post a Comment